የጂዮሎጂስት ፕሮፌሰር ብስራት ይባስ ባብሳ ጉብኝት በቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ

የጂዮሎጂስት ፕሮፌሰር ብስራት ይባስ ባብሳ ጉብኝት በቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ
ታህሣሥ 2014 ዓ.ም
ፕሮፌሰር ብስራት ይባስ ባብሳ በደቡብ አፍሪካ የ"University of Free State" ተመራማሪ እና የስነ-ምድር ጥናት (Geology) ትምህርት ክፍል ሀላፊ ሲሆኑ፤ወደ ሀገራቸው በመመለስ በቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ ጉብኝት አደርገዋል ።
ታህሣሥ 12/2014 ዓ.ም-(የቡሌ ሆራ ህዝብ ግኑኝነት ዳይሬክቶሬት)
ፕሮፌሰር ብስራት ይባስ ባብሳ ሀገራችን ኢትዮጵያ ካፈራቻቸዉ የስነ-ምድር ጥናት(Geology) እና የማዕድን ልማት(Mining) ምህራን መካከል አንዱ ሲሆኑ የPhD ጥናታቸውን ያደረጉትም ለዘርፉ ጥናትና ምርምር ምቹ መልከዓ-ምድር ባለው በጉጂ ዞን ለገደንቢና ሳካሮ ነዉ።
University of Free State በደቡብ አፍሪካ ከሚገኙ አንጋፋ ዩኒቨርሲቲዎች መካከል አንዱ ሲሆን ፕሮፌሰር ብስራት ይባስም በዚሁ ዩኒቨርሲቲ የGeology ትምህርት ክፍል ሀላፊ ሆነው በመሥራት ላይ ይገኛሉ።
የቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ማህበረሰብ አገልግሎት ምክትል ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጉሚ ቦሩ እንደገለጹት የቡሌ ሆራ ዩኒቨርስቲ የሚገኝበት መልከዓ-ምድር በተፈጥሮ ሀብቶች እና የከበሩ ማዕድናት የበለጸገ በመሆኑና ዩኒቨርሲቲው በዘርፉ ላይ ጥልቀት ያለው ጥናትና ምርምር ስራዎችን ለመሥራት ዘርፉን የትኩረት አቅጣጫዉ አድርጎ አቅዶ እየሠራ ይገኛል ።
እንዲሁም ዩኒቨርሲቲዉ የዘርፉን ምሁራን ከያሉበት በማፈላለግና በመጻጻፍ ብሎም አብሮ ለመሥራት ዘርፈ ብዙ ሥራዎች እየተከናወኑ ናቸው ። ፕሮፌሰር ብስራት ይባስ ከነዚህ ምሁራን ዉስጥ አንዱ ሲሆኑ ከተቋሙ ጋር አብሮ ለመስራት ስምምነት ላይ ተደርሷል ብለዋል ዶ/ር ጉሚ ቦሩ።
ፕሮፌሰር ብስራት ይባስ በመምህርነትና በስነ-ምድርና ማዕድን ጥናት (Geological servey) ለረጅም ጊዜ የካበተ ልምድና ዕውቀት ባለቤትም ናቸው ።
ዶ/ር ጉሚ ቦሩ አክለዉ ዩኒቨርሲቲዉ ከፕሮፌሰር ብስራት ይባስ ጋር በበይነ መረብ(online) የመማር ማስተማር ሥራ ለማካሄድ፣በምርምር ሥራ እንዲሁም በተለያዩ አጫጭር ቴክኒካዊና ሳይንሳዊ ስልጠናዎች ዙሪያ በጋራ ለመስራት ሰምምነት ላይ መደረሱን ገልጸዋል ።
የስነ-ምድር ጥናት(Geology) እና የማዕድን ልማት(Mining) ቤተ-ሙከራዎች ምልከታ ያደረጉት ፕሮፌሰር ብስራት ይባስ ዩኒቨርስቲው ለዘርፉ የሰጠውን ትኩረትና ተቋማዊ ለዉጡን በማድነቅ በጋራ ለመስራት ፈቃደኛ መሆናቸውን ገልጸዋል። ለፕሮፌሰር ብስራት ይባስ ባብሳ "የቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ በጣም ምርጥ ዩኒቨርሲቲ ነዉ። ለላቀ ለዉጥ የቆመ እና የሚተጋ አመራር ያለዉ ተቋም እና ወጣት ምሁራን ያለዉ መሆኑ ተመራጭ ያደርገዋል ።
"Bule Hora University is an interesting University!" Professor Bisrat Yibas Babsa
ለትምህርት ክፍሎቹ ምሁራን "በቆይታችሁ ጊዜ ዉስጥ ለዩኒቨርሲቲያችሁ የራሳችሁን ሌጋሲ አስቀምጡ!" በማለት ምክር ለግሰዋል ።
በጉብኝቱ ዶ/ር ታምሩ አኖሌ የቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ አካዳሚክ ጉዳዮች ም/ፕሬዝዳንት እና የፕሬዝዳንት ተወካይ፣ዶ/ር ጉሚ ቦሩ የቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ማህበረሰብ አገልግሎት ምክትል ፕሬዚዳንት፣ አቶ ዳንኤል ሠይፉ የቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር እና የስነ-ምድር ጥናት(Geology) እና የማዕድን ልማት(Mining) ትምህርት ክፍሎች ምሁራን ተገኝተዋል ።
ዶ/ር ታምሩ አኖሌ የቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ አካዳሚክ ጉዳዮች ም/ፕሬዝዳንት እና የፕሬዝዳንት ተወካይ ስለጉብኝታቸው እና አጋርነታቸው ለፕሮፌሰር ብስራት ይባስ ባብሳ አድናቆታቸውን በመግለጽ በራሳቸዉና በዩኒቨርሲቲዉ ስም ልባዊ ምስጋና አቅርበዋል ።
ለላቀ ለዉጥ እንተጋለን !!!
የቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ